አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2017(ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በኅብር የተገነባ የኢትዮጵያ የማንሰራራት መገለጫና የይቻላል ማሳያ መሆኑን የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ፣ የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ እና የአዲስ አበባ የህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ምክር ቤት ሰብሰቢ ጃንጥራር ዓባይ ገለጹ።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መመሪያ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሠላም ዋንጫን ለኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን አስረክቧል።
ዋንጫንው የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሌተናል ጄኔራል ድሪባ መኮንን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ጌቱ አርጋው እጅ ተረክበዋል።
የርክክብ ሥነ-ስርዓቱ "ታላቁ የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ጀምረን የመፈፀማችንና የመቻላችን ማሳያ፥ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት የአንድነታችን አርማ" በሚል መሪ ሃሳብ ተካሂዷል።
የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ፣ የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊና የአዲስ አበባ የህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ምክር ቤት ሰብሰቢ ጃንጥራር ዓባይ በዚሁ ወቅት፥ ህዳሴ ግድብ ቅድመ አያቶች ኢትዮጵያን በደማቸው እንዳጸኗት ሁሉ የአሁኑ ትውልድ ሀገሩን በላቡ የሚያለማበት የጋራ ፕሮጀክት ነው ብለዋል።
የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክትም በሁሉም ዜጎች የፋይናንስ ምንጭ ድጋፍና ትብብር የተገነባ የኢትዮጵያ የማንሰራራት መገለጫና የይቻላል ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርም ለፕሮጀክቱ ግንባታ እስካሁን ከ6 ነጥብ 1 ቢሊየን ብር በላይ የቦንድ ግዥና የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ የጸጥታ መዋቅር የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት በሚገነባበት ስፍራ የአካባቢውን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ ታሪክ የማይዘነጋው አሻራ እያሳረፉ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ዋና ስራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሔ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያውያን በህዳሴ ግድብ የግንባታ ሂደቱ ሁሉም ኢትዮጵያውያን በሁሉም ዘርፍ ያደረጉት ያላሳለሰ ድጋፍ በትውልድ ቅብብሎሽ ሲዘከር የሚኖር ታሪካዊ የድል አርማ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያውያን በታላቁ ህዳሴ ግድብ የእስካሁኑ የግንባታ ሂደት ከ23 ቢሊየን ብር በላይ የገንዘብ ድጋፍ መደረጉን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ጌቱ አርጋው፥ የህዳሴ ግድብ የሠላም ዋንጫን ከኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በመረከብ በሁሉም ክፍለ ከተሞች የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ሲካሄድ መቆየቱን አስታውቀዋል።
ፕሮጀክቱም የኢትዮጵያ የመነሳት ዘመን እረፍት የነሳቸውን በርካታ የውስጥና የውጭ ታሪካዊ ጠላቶችን ሴራ በመሻገር በአሸናፊነት ጉዞ እንድትገኝ እያስቻላት እንደሚገኝ ተናግረዋል።
የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሌተናል ጄኔራል ድሪባ መኮንን፥ የክልሉ የፖሊስ ሰራዊት አባላት ከፌደራል የጸጥታ ተቋማት ጋር በመተባበር የክልሉን ሰላምና ደህንነት ከማስጠበቅ በተጨማሪ በልማት መስክም ንቁ ተሳታፊ መሆኑን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሠላም ዋንጫን በ2016 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በመረከብ ለግድቡ ግንባታ ስኬት የገንዘብ ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል።
አሶሳ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ):- ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልዱ አሻራና ኩራት ነው ሲሉ የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አብዱልሙህሲን ሐሰን...
Feb 28, 2025
ሚዛን አማን፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማ በመ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4 /2017(ኢዜአ)፦ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በግብርናው ዘርፍ እያከናወነ ያለው በምርምር የተደገፈ ስራ ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ም...
Feb 12, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ማዕከል መገንባት በክልሉ ለግብርና ስራው መሠረታዊ የሆነ...
Feb 8, 2025