የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የኩታ ገጠምና በመስመር የመዝራት የግብርና ስነ-ዘዴን በመጠቀም ምርታማነታችንን ለማሳደግ እየሰራን ነው- አርሶ አደሮች

Jul 22, 2025

IDOPRESS

ደብረ ማርቆስ ፤ሐምሌ 14/2017(ኢዜአ)፦የኩታ ገጠምና በመስመር የመዝራት የግብርና ስነ-ዘዴን በመጠቀም ምርታማነታችንን በማሳደግ ተጠቃሚነታችንን ለማጎልበት እየሰራን እንገኛለን ሲሉ በምስራቅ ጎጃም ዞን የባሶ ሊበን ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ።

በምስራቅ ጎጃም ዞን በባሶሊበን ወረዳ በልምጭም ቀበሌ ስንዴን በኩታ ገጠምና በመስመር የመዝራት ተግባር ዛሬ ተጀምሯል።


በተግባሩ ላይ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች መካከል ይልቃል ጌቴ እንደገለጹት ከአንድ ሄክታር በላይ መሬታቸውን የኩታ ገጠም የግብርና አሰራርን ተጠቅመው ስንዴ መዝራት መጀመራቸውን ተናግረዋል።


የኩታ ገጠም አሰራር ግብዓትን በተሟላ ሁኔታ በመጠቀም፣ በጋራ በማረምና ተባይን በመከላከል ምርትና ምርታማነታቸው እንዲጨምር እያደረገ በመምጣቱ በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል።

ስንዴን በኩታ ገጠም ማልማት ከጀመሩ ከሁለት ዓመት በላይ እንደሆናቸው ጠቁመው በሄክታር ከስምንት ኩንታል በላይ የምርት ጭማሪ እንዳስገኘላቸውም አስረድተዋል።

የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ባምላኩ ጫኔ በበኩላቸው በምርት ዘመኑ ከአንድ ሄክታር በላይ መሬታቸውን በኩታ ገጠምና በመስመር አሰራር ስንዴ መዝራት መጀመራቸውን ተናግረዋል።


ካለፈው ዓመት ጀምሮ ስንዴን በኩታ ገጠም እያለሙ መሆኑን ገልጸው ቴክኖሎጂንና አዳዲስ አሰራሮችን በመጠቀም ከአምስት ኩንታል በላይ የምርት ጭማሪ እንዳገኙም ገልጸዋል።

ያገኙትን ጥቅም ለማስፋትም በዛሬው እለት በኩታ ገጠምና በመስመር ስንዴ መዝራት መጀመራቸውን አስረድተዋል።

የምስራቅ ጎጃም ዞን ግብርና መምሪያ ተወካይ ኃላፊ አቶ ሃብታሙ አህመድ እንዳሉት በምርት ዘመኑ በመኸር ከሚለማው ከ642 ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ ከ435 ሄክታር በላዩን በኩታ ገጠም የማልማት ስራ ተጀምሯል።


ከ90 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ በሚካሄደው ልማት ላይም ከ168 ሺህ በላይ የሚሆነው በስንዴ ሰብል ለመሸፈን እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ምርታማነትን በማሳደግም ከ8 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ለመሰብሰብ የሚያስችል በኩታ ገጠምና በመስመር የመዝራት ዘዴ ዛሬ መጀመሩን አስታውቀዋል።

የዞኑ አስተዳዳሪ አማካሪ አቶ ሙሉቀን ቢያድግልኝ በበኩላቸው ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ለወጪ ንግድና ለኢንዱስትሪ የሚሆን ምርት ለማምረት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል።


በዚህም ቴክኖሎጂን፣ ግብዓትንና አዳዲስ አሰራሮችን በተሟላ መልኩ ለመተግበር በተደረገ ጥረትም ከ908 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ቀርቦ እየተሰራጨ መሆኑን አመልክተዋል።

በዞኑ በ2017/18 የምርት ዘመን በአጠቃላይ በዘር ከሚሸፈነው ማሳ ከ25 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እየተሰራ መሆኑን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.