የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርብቶና አርሶ አደሩን ሕይወት በመቀየር ላይ የሚገኙ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ -የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች

Jul 10, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርብቶና አርሶ አደሩን ሕይወት በመቀየር ላይ የሚገኙ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ፡፡

የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ እና የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ባለፉት አምስት ቀናት በክልሉ አምስት ዞኖች ያደረጉት ጉብኝት ስኬታማ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡


በክልሉ ፕሬዚዳንት የተመራ ቡድን በቦረና፣ በምዕራብ ጉጂ፣ በምስራቅ ቦረና፣ በጉጂ እና በባሌ ዞኖች የመስክ ምልከታ አድርገዋል።

በተለይም በቦረና፣ በምዕራብ ጉጂ፣ በምስራቅ ቦረና እና በጉጂ ቆላማ አካባቢዎች ለዘመናት ያለሙ መሬቶችን በማልማት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ አስደናቂ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡

በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ከፍያለው ተፈራ እንዳሉት መንግስት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ተረጂነትን ለማስቀረት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል፡፡

በክልሉ ያሉ ጸጋዎችን በመለየት ምርታማነትን ለማሳደግ በግብርናው ዘርፍ በስንዴ ልማትና በሌማት ትሩፋት ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

ለአብነትም በቦረና ዞን ከዚህ ቀደም ባልተለመደ መልኩ ስንዴ በክላስተር መመረት መጀመሩ መልካም ጅማሮ መሆኑን ገልጸው ይህም ተረጂነትን ለማስቀረት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡


በምክትል ፕሬዚዳንት ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ ሳዳት ነሻ በበኩላቸው የክልሉ መንግስት ከተረጂነት የመላቀቅን ግብን ወደ ህዝቡ በማውረድ በሙሉ አቅሙ ወደ ምርት እንዲገባ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡

በዚህም በምስራቅ ቦረና ዞን ከ60ሺህ ሄክታር በላይ ስንዴ በማምረት ከዚህ ቀደም ባልተለመደ መልኩ ምርታማነት እየተረጋገጠ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ይህም በአከባቢው የምግብ ዋስትናን በራስ አቅም ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡


የኦሮሚያ ክልል ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ኃይሉ አዱኛ፣ ጉብኝቱ ከተረጂነት ለመላቀቅ ምርታማነትን ለማሳደግ የተያዙ ግቦችን አፈጻጸም በመመልከት ውጤታማ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አቅጣጫ የተሰጠበት መሆኑን አንስተዋል።

በተለይም በቦረና እና ጉጂ አከባቢዎች በስፋት የሚታየው ስንዴ ምርት ከተረጂነት ለመላቀቅ የተጀመሩ ስራዎችን የሚያፋጥኑ ትልቅ ብስራት ናቸው ብለዋል፡፡

ከተረጂነት ለመላቀቅ የተነደፉ ፖሊሲዎች በተጨባጭ መሬት ላይ ውጤት እያመጣ መሆኑንም ጉብኝቱ አመላክቷል ብለዋል፡፡

በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርብቶና አርሶ አደሩን ሕይወት በመቀየር ላይ የሚገኙ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.