አዲስ አበባ፤ሐምሌ 10/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የማዳበሪያና ምርጥ ዘር ግብዓት እና ማሽነሪዎችን አቅርቦት በማሻሻል ምርታማነትን ማሳደግና የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችል ገንቢ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ገለጸ።
የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ከቻይና ዓለም አቀፍ ሲኖትራክ ኩባንያ ጋር የጭነት ሲኖትራክ ተሽከርካሪዎችን በመግዛት ወኪል አቅራቢ መሆን የሚችልበትን ስምምነት ይፋ አድርጓል።
የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ክፍሌ ወልደማርያም በዚህ ወቅት እንዳሉት፥ ስምምነቱ የዓለም አቀፉን የሲኖትራክ የጭነት ተሽከርካሪዎች ወደ ሀገር ውስጥ በማስገባት ለገበያ ማቅረብ የሚያስችል ውክልና ነው።
ይህም በሁለቱ የልማት ድርጅቶች መካከል ያለውን አጋርነት በማሳደግ የንግድ ግንኙነታቸውን የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል።
ስምምነቱ በሁለቱ የልማት ድርጅቶች መካከል ላለው የጋራ ራዕይና መተማመን ማሳያ ነው ብለዋል።
ግብርና የአብዛኛው ህዝብ የኑሮ መሰረትና ለኢኮኖሚው ጉልህ ሚና ያለው መሆኑን ገልጸው፤ የዘርፉን እምቅ አቅምና ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣውን ፍላጎት ለማሟላት የትራንስፖርት ዘርፉን ማዘመን፤ ውጤታማ የሎጂስቲክና አገልግሎት ሰንሰለት መፍጠር ያስፈልጋል ብለዋል።
ኮርፖሬሽኑ ግብዓቶችን በማቅረብ የግብርናውን ዘርፍ ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ስምምነቱ ኢትዮጵያ በግብርና እና በትራንስፖርት ዘርፍ እያስመዘገበች ላለው ተጨባጭ ለውጥ ተጨማሪ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
በመሆኑም የሲኖትራክ ተሽከርካሪዎች የአፈር ማዳበሪያን፣ ምርጥ ዘር፣ የግብርና ማሽነሪዎችን እና ሌሎች ግብዓቶችን በፍጥነትና በጥራት ለተጠቃሚዎች ለማድረስ የጎላ አበርክቶ ይኖራቸዋል ነው ያሉት።
የሲኖትራክ ኢንተርናሽናል ምክትል ፕሬዝዳንት ዛዮ ሁዋ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክ አገልግሎት በቀጣናው ሰፊና ምቹ በመሆኑ ከኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ጋር በአጋርነት ለመስራት ተስማምተናል ብለዋል።
የሲኖትራክ ኢንተርናሽናል ኩባንያ በዓለም ዙሪያ በርካታ አጋር ድርጅቶች እንዳሉት በመግለጽ፤ ለኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን በርካታ ተሽከርካሪዎች እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል።
ለዚህ የሚመጥን የመለዋወጫ እና ሌሎች አገልግሎቶችን በስፋት እንደሚያቀርቡ በመጥቀስ ትብብራቸው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
ስምምነቱ የኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ግቦችን በማሳካት ለግብርና ምርትና ምርታማነት ገንቢ አስተዋጽኦ ከማበርከት ባለፈም መልካም ትብብርም ይፈጥራል ነው ያሉት።
በኢትዮጵያ እና ቻይና መካከል ያለውን ትብብር በማጠናከር የቤልት ኤንዴ ሮድ ኢኒሼቲቭን ለማሳደግ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረውም ተናግረዋል።
አዲስ አበባ፤ የካቲት 21/2017(ኢዜአ)፡- የምግብ ዋስትና እና ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ለነገ የሚተው የምርጫ ጉዳይ ባለመሆኑ በልዩ ትኩረት መረባረብ እንደሚገባ...
Feb 28, 2025
ሐረር፤ የካቲት 16/2017(ኢዜአ)፦ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ ሁሉን አቀፍ ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ ጥር 30/2017(ኢዜአ)፦የየካቲት ወር የነዳጅ ምርቶች የችርቻሮ መሸጫ ዋጋ በጥር ወር በነበረበት የሚቀጥል መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስ...
Feb 8, 2025