የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ዝግጅቱ ተጠናክሮ ቀጥሏል - የክልሉ ግብርና ቢሮ

May 13, 2025

IDOPRESS

አዳማ፤ ግንቦት 4/2017(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ዘንድሮ ለሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር እየተደረገ ያለው ዝግጅት ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

የቢሮው ምክትል ሀላፊ ኤሊያስ ከድር ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብሩን በስኬት ለማከናወን ከችግኝ ዘር አቅርቦት ጀምሮ ስብጥሩን በጠበቀ መልኩ እየተሰናዳ ነው።

በዚህም በተለይ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የሚያግዙና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው እንደ ሀገር በቀል ዛፎች፣ ፍራፍሬና የእንስሳት መኖ ችግኝ ትኩረት እንደተደረገባቸው ጠቅሰዋል።

በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከተዘጋጀው ችግኝ ውስጥ 11 በመቶ ለምግብነት የሚያገለግል አቮካዶ፣ ሙዝ፣ ፓፓያ፣ ዘይቱን፣ ቴምርና ማንጎን ጨምሮ በፍጥነት ምርት የሚሰጡ የተለያዩ ዝርያዎች መሆናቸውን ተናግረዋል።

ቀሪው ለደን ልማትና ለሌሎችም አገልግሎቶች የሚውሉ መሆናቸውን አስረድተዋል።

በክልሉ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላውን ከ1 ሚሊዮን ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ለማከናወን ታቅዶ የተከላ ቦታ ልየታና የጉድጓድ ዝግጅት ስራ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛልም ነው ያሉት።


የክልሉ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሰይፈዲን መሃዲ በበኩላቸው፤ በችግኝ ጣቢያዎች የሚዘጋጀው ችግኝ ያለበትን ሁኔታ በየጊዜው በመስክ እየገመገሙ ለተከላ መድረሱን እያረጋገጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የሀገር በቀል ዛፎች ዝሪያን ለመጠበቅ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የችግኝ ዝግጅት ልዩ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል።

በተለይ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማትን እውን ለማድረግና የደን ሽፋኑን በአስተማማኝ ለማሳደግ የሀገር በቀል ዛፎች ሚና የጎላ መሆኑን ጠቅሰው፤ የደጋ ፍራፍሬ በተለይ የአፕል ችግኝ በስፋት መዘጋጀቱን አመላክተዋል።

የክልሉን የደን ሽፋን ለማሳደግ ግብ መቀመጡን ጠቁመው፤ ለዚህም የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል።

ተከላ የሚጀመርበት ወቅት እየተቃረበ በመሆኑ የጉድጓድና ሌሎች ተጓዳኝ ዝግጅቶች ተጠናክረው መቀጠላቸውንም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.