የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ለትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ መሰረት በመሆኑ ህዝቡ የጀመረውን ተሳትፎ ማጠናከር አለበት - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ

Jul 31, 2025

IDOPRESS

ሁምቦ፤ ሐምሌ 24/2017(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር ለትውልድ የተሻለች ሀገርን ለማስረከብ መሰረት በመሆኑ ህዝቡ የጀመረውን ተግባር አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ።

ርዕሰ መስተዳድሩ በወላይታ ዞን ሁምቦ ወረዳ ሶልኳ ተራራ ላይ የዘንድሮን የአንድ ጀንበር የአረንጓዴ ዐሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አስጀምረዋል።


በዚህን ወቅት ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት በህብረተሰቡ ተሳትፎ የተራቆቱ ቦታዎችንና ተራሮችን ለማልማት የተጀመረው ሥራ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተጀመረው ኢትዮጵያን አረንጓዴ የማልበስ ተግባር ኢትዮጵያን በዓለም ምሳሌ እያደረጋት መሆኑንም ገልጸዋል።

ችግኝ መትከል የመሬት ለምነትን ከማስጠበቅ፣ ድርቅን ከመከላከልና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከሚኖረው ፋይዳ ባለፈ ለወጣቶች የሥራ ዕድል እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል።

በወላይታ ዞን ሁምቦ ወረዳ ሶልኳ ተራራ ዛሬ የተተከሉ ችግኞች ከግብ እንዲደርሱ ሁሉም ሰው የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ ኃላፊነቱን እንዲወጣ አስገንዝበዋል።

በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪ እና የግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ(ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሀ ግብር እየተካሄደ ይገኛል ብለዋል።

የተራቆቱ ተራሮችን ለመታደግ የአካባቢው ህዝብ ለአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር ስኬታማነት መረባረብ አለበት ሲሉም ኃላፊው ተናግረዋል።

ችግኝ መትከል ያለውን ጠቀሜታ የተረዳ ማህበረሰብ የመፍጠር ውጥን ከግብ እየደረሰ ስለመሆኑ የዛሬው መርሃ ግብር ማሳያ ነው ብለዋል።

የተፈጥሮ ሚዛንን ለማስጠበቅ የተጀመረው ይህ ሥራ የሁል ጊዜ ተግባር ሆኖ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስገንዝበዋል።

የአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በዞኑ የተመናመኑ ደኖችና ተራሮች ለምተው ለኑሮ ምቹ አካባቢ እየተፈጠረ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ተሰማ ናቸው።

የአየር ንብረት መዛባትን በመቋቋም ለነገው ትውልድ የለማች ሀገር ለማስረከብ መሰረት ለሆነው የአረንጓዴ ልማት መጠናከር ህብረተሰቡ እያደረገ ያለውን ንቁ ተሳትፎ እንዲያጠናክርም አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.