የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

መንግሥት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 32 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል - አቶ ማሞ ምህረቱ

Jul 23, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 15/2017(ኢዜአ)፦ መንግስት የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው በፈጠረው ምቹ ሁኔታ ከሁሉም ምንጮች 32 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምህረቱ ገለጹ።

የግሉ ዘርፍ ተዋናዮችን፣ ፖሊሲ አውጪዎችንና የፋይናንስ ተቋማትን በማሳተፍ በዘላቂ ልማት፣ በማክሮ ኢኮኖሚ፣ በመዋቅራዊና በንግድ ዙሪያ የሚመክረው የኢትዮጵያ የፋይናንስ ጉባኤ የግል ዘርፍ መድረክ እየተካሄደ ነው።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምህረቱ በዚህ ወቅት፣ የተረጋጋ የማክሮ ኢኮኖሚ እና ቀጣይነት ያለው የሀገር ዕድገትን ለማረጋገጥ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፖሊሲ ገቢራዊ መደረጉን ገልጸዋል።

በዚህም የዋጋ ግሽበትን በግማሽ መቀነስ፣ የውጭ ምንዛሪ በገበያ እንዲወሰን በማድረግ የምንዛሪ ክምችትን ማሳደግ እንዲሁም በመሰረታዊ ዘርፎች ላይ ምርታማነትን መጨመር ተችሏል ብለዋል።

የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያውም አስደናቂ ውጤት ማምጣቱን ጠቅሰው፥ ዘመናዊና ለልማት የሚመች የፋይናንስ ዘርፍ እንዲኖር ምቹ ሀኔታ እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል።

መንግስት በ2016 በጀት ዓመት ከሁሉም ምንጮች ያገኘው የውጭ ምንዛሪ ግኝት 24 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር እንደነበር አስታወሰው፣ ከተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ወዲህ በ2017 በጀት ዓመት 32 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን ገልጸዋል።

የሀገር እድገት በመንግስት ብቻ የሚረጋገጥ አይደለም ያሉት የባንኩ ገዥ፤ የግሉ ዘርፍ የነቃ ተሳትፎና ትብብር ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል።

የዛሬው ጉባኤም የግሉ ዘርፍ በመንግሥት ፖሊሲዎች ላይ ግልጽነት በመፍጠር በሁሉም ዘርፎች የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማስቀጠል ምክክር የሚደረግበት መሆኑን ገልጸዋል።

የፕላንና ልማት ሚኒስቴር፣ የገንዘብ ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በትብብር ባዘጋጁት ጉባኤ የመንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የባንክ ፕሬዝዳንቶችና የተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት መሪዎች ታድመዋል።

የማክሮ ኢኮኖሚ መዋቅራዊ ማሻሻያ፣ የፋይናንስ ዘርፍ ሪፎርምና የኢንቨስትመንት ዕድሎች፣ ለአካታች ፋይናንስና ልማት የብድር አገልግሎት ማመቻቸት፣ የኢንቨስትመንት ከባቢ በኢትዮጵያ እና የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ በመርሀ ግብሩ የፓናል ውይይት የሚደረግባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ናቸው።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.