የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የግብርናውን ዘርፍ እድገት ለማስቀጠል የምርምር ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ-የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዮት

Jul 7, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ሰኔ 27/2017(ኢዜአ)፦የግብርናውን ዘርፍ እድገት ለማስቀጠል የተጀመሩ የምርምር ስራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዮት ገለፀ።

ኢንስቲትዮቱ በቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ የ2017 አረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር አካሂዷል።

በቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል የተለቀቁ ቴክኖሎጂዎችን የሚያሳይ ኤግዚቢሽንም ከፍቷል።


የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ንጉሴ ደቻሳ (ፕ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን እየሰራ ነው።

የተሻሻሉ ዝርያዎችን በማውጣት የማባዛትና ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ፣ በአስተራረስና አመራረት ሂደት ዘዴዎች ላይ ክህሎት የማሳደግ ስራ እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።

ኢንስቲትዩቱ ባሉት 23 ማዕከላት የተለያዩ የምርምር ስራዎችን በማከናወን ዘርፉን የመደገፍ ስራ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤በቀጣይም የግብርናውን እድገት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አብራርተዋል።

በኤግዚቢሽኑ የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከልም የተለያዩ ምርምሮችን በማካሄድ የሰብልና እንስሳት ዝርያዎችን የማባዛትና ተደራሽ የማድረግ ስራ እያከናወነ መሆኑን መመልከታቸውን ገልፀዋል።

ኢንስቲትዩቱ ዛሬ በቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ማስጀመሩን አንስተው፤ በ23ቱም ማዕከላት መርሃግብሩ እንደሚከናወን ጠቁመዋል።

የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ ችግኞችን በመትከል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ነው ብለዋል።


የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር ዳኜ ሞጆ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ከ70 ዓመት በላይ በተለያዩ ሰብልና እንስሳት ላይ ምርምር በማድረግ ዝርያዎችን ሲያሻሽል መቆየቱን ገልጸዋል።

ያከናወናቸው ተግባራት ለግብርናው ዘርፍ እድገት አስተዋፅኦ ያላቸው እንደሆኑም ተናግረዋል።

በማዕከሉ በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉት የአቮካዶና ፓፓዬ የቡናና ወይራ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል።

የማዕከሉ የጤና ስፖርት ማህበር ሊቀ መንበር ግዛቸው ካባ እና የሰው ሀብት ክፍል ሰራተኛ የሆኑት ወይዘሮ ድንቅነሽ አየለ፤ ዕጽዋቱ የአካባቢ ስነ ምህዳርን ለመጠበቅ የሚረዱ መሆናቸውን ጠቁመው፤ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በመንከባከብ ለፅድቀት ለማድረስ የበኩላቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.