የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የኢንዱስትሪ ምርታማነትን የሚያሳልጥ የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ምኅዳር ተፈጥሯል-ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር)

May 8, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 29/2017(ኢዜአ)፦የኢንዱስትሪን የማምረት አቅም የሚያሳልጥ የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ምኅዳር መፈጠሩን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር) ገለጹ።


የኢትዮጵያ ታምርት አምስተኛ ቀን የፓናል ውይይት መድረክ ተካሄዷል።


መድረኩ የአራተኛው ኢንዱስትሪ አብዮት መገለጫ የሆነው የሰው ሰራሽ አስተውሎት በአምራች ኢንዱስትሪው የምርት ሂደት ላይ እንዴት መጠቀም እንደሚቻል እና የምርት ሂደት እና ምርታማነትን ማቀላጠፍ ስለሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ያተኮረ ነው።


እንዲሁም የምርምር እና የትምህርት ተቋማት እነዚህን በስርዓተ ትምህርትና በምርምር ስራዎች በማካተት እንዲሁም ከኢንዱስትሪዎች ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት በማድረግ ተግባር ተኮር የሆነ ስራዎችን የሚሰሩበት መንገዶች ላይ አተኩሯል።


በተጨማሪም ከቴክኖሎጂ እድገት ፈጣንነት እና ተለዋዋጭነት አንፃር ኢትዮጵያ በዚህ ዘርፍ ላይ ስለሚኖራት ተጠቃሚነት የሚዳሥሥ ነው።


የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ለኢንዱስትሪው ዘርፍ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመዋል።


በዚህም የዘርፉን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የመሰረተ ልማቶች ግንባታ፣ ኮኔክቲቪቲ እንዲሁም የተለያዩ ፕላትፎርሞች መፈጠራቸውን አንስተው፤ ስታርታፖችም ለአምራች ዘርፉ ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።


የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሽኔ የትምህርት ተቋማት የፈጠራ ማእከል እንዲሆኑ የስርዓተ ትምህርት ዝግጅት ሪፎርምን ጨምሮ ሌሎች ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል።


ተማሪዎችም በዘርፉ ተወዳዳሪ የሚሆኑበት የተለያዩ የትምህርት መርሀ ግብሮች ተቀርጸው ተግባራዊ መደረጋቸውን ገልጸዋል።


የአምራች ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሚልኬሳ ጃገማ (ዶ/ር) በቴክኖሎጂ ዘርፍ የሰለጠነ የሰው ሀይል እጥረት አንዱ ተግዳሮት መሆኑን ገልጸዋል።


ኢንስቲትዩቱ በዘርፉ አቅም የመገንባት ስራ እንዲሁም የዘርፉን ተዋንያን በማማከር እና በማሰልጠን በርካታ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑንም ጠቁመዋል።


የአዲስ አበባ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ደረጀ እንግዳ (ዶ/ር) ዩኒቨርሲቲው የዘርፉን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።


በዩኒቨርሲቲው የሚከናወኑ የምርምር ስራዎች የኢንዱስትሪውን ተወዳዳሪነት የሚያጎለብቱ መሆኑንም ገልጸዋል።


በሰው ሰራሽ አስተውሎት ስራ ላይ የተሰማራው የፋኖስ ቴክ መስራች እና ባለቤት ወጣት ቴዎድሮስ ስንታየሁ ቴክኖሎጂ የቅንጦት ጉዳይ አለመሆኑን ገልጾ፤ በአምራች ኢንዱስትሪ ላይ የሚተገበሩ ቴክኖሎጂዎች ለምርታማነት መጨመር ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ነው የተናገረው።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.