
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 10/2017(ኢዜአ)፦ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር 6 ነጥብ 3 ቢሊዮን የዶሮ እንቁላልና 192ሺህ ቶን የአሳ ምርት መመረቱን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ።
የዶሮ ስጋና እንቁላል ምርታማነትን ለማስፋትም 90 ሚሊዮን የአንድ ቀን ጫጩት ለህብረተሰቡ መሰራጨቱን ሚኒስቴሩ ገልጿል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሌማት ትሩፋት መርሐ ግብርን ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም በአርባ ምንጭ ከተማ ማስጀመራቸው ይታወሳል።
የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፥ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ ትልቅ ውጤት ተገኝቷል።

መርሐ ግብሩ የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ፣ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥና የምግብ ስርዓትን ማሻሻል ላይ ከፍተኛ ለውጥ ማምጣቱን ተናግረዋል።
የሌማት ትሩፋት ትኩረት ካደረገባቸው መካከል የዶሮ ስጋ እና የእንቁላል ምርትን ለማሳደግ የአንድ ቀን ጫጩት ስርጭትን ማስፋት ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።
በዚህም በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 90 ሚሊዮን የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩት ለህብረተሰቡ መሰራጨቱን ገልጸው፥ ይህም ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከእጥፍ በላይ መሆኑን አንስተዋል።
በዶሮ ስጋና በእንቁላል ምርትም ከፍተኛ አፈጻጸም መኖሩን ጠቅሰው፥ 6 ነጥብ 3 ቢሊዮን እንቁላል እና 128ሺህ ቶን የዶሮ ስጋ መመረቱን አስረድተዋል።

ሌላኛው በሌማት ትሩፋት ትኩረት የተሰጠው የአሳ ምርት ሲሆን፥ ህብረተሰቡ ከውሃ አካላትና ከኩሬዎች በተጨማሪ በየአካባቢው፣ በጓሮው፣ በአነስተኛ ቦታ አሳ እንዲያመርት ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው ብለዋል።
በዚህም የአሳ ማስፈልፈያ ማዕካለትን በማጠናከርና አዳዲስ በመጨመር የአሳ ጫጩት የሚያጓጉዙ ዘመናዊ ተሽከርካሪዎችን በመጠቀም የስርጭት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ነው ያነሱት።
በባህርዳር፣ በባቱ፣ በአርባ ምንጭ፣ በሐዋሳ እና በሰበታ የአሳ ጫጩት ማስፈልፈያ ማዕከላትን የማጠናከር ስራዎች እንደተከናወኑም ጠቁመዋል።

የአሳ ምርት አቅርቦት እያደገ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 192 ሺህ ቶን የአሳ ምርት መገኘቱን ተናግረዋል።
ይህን ለማጠናከርም 8 ነጥብ 3 ሚሊዮን የአሳ ጫጩት ስርጭት መከናወኑንም ሚኒስትር ዴኤታው ጨምረው ገልጸዋል።
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ባለፉት 10 ወራት ከወጪ ንግድ 8 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁ...
May 15, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡-የጉምሩክ አዋጅ ረቂቅ ማሻሻያ የወጪና የገቢ ንግድን ለማሳለጥ የጎላ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው በህዝብ ተወካዮች ምክር ...
Apr 23, 2026
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) በኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራ ዙሪያ ያላቸውን ትብብር ይበልጥ ለማጎ...
Apr 17, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦ የሀረሪ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት በጀጎል አለም አቀፍ ቅርስ ውስጥ የሚገነባው የ''ዳር ሀረር'' መልሶ ማልማት ፕሮ...
Apr 12, 2026