የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በሰሜን ወሎ ዞን በበጋ መስኖ ከለማው የስንዴ ሰብል የደረሰው እየተሰበሰበ ነው

Apr 14, 2025

IDOPRESS

ወልዲያ ፤ ሚያዝያ 4/2017(ኢዜአ)፡- በሰሜን ወሎ ዞን በዘንድሮ የበጋ ወቅት በ20 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከለማው የስንዴ ሰብል ውስጥ የደረሰው እየተሰበሰበ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ።

እስካሁንም በአምስት ሺህ 625 ሄክታር መሬት ላይ የደረሰ የስንዴ ሰብል መሰብሰቡን መምሪያው ገልጿል።

በመምሪያው የአትክልት፣ ፍራፍሬና መስኖ ቡድን መሪ አቶ አለባቸው መራዊ፤ በመስኖ እየለማ ያለው የበጋ ስንዴ ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳዳገው እንደሚገኝ ለኢዜአ ተናግራል።

በዚህም በዘንድሮው የበጋ ወቅት በተካሄደው የመስኖ ልማት ከተሸፈነው 20 ሺህ ሄክታር መሬት የስንዴ ሰብል ላይ ከ728 ሺህ ኩንታል በላይ ምርትም እንደሚጠበቅ ገልጸዋል።

እስካሁን በተደረገው ጥረትም በአምስት ሺህ 625 ሄክታር የተዘራውን ሰብል በመሰብሰብ 212 ሺህ ኩንታል ምርት ማምረት መቻሉን አስታውቀዋል።


በበጋ ስንዴ ልማቱ እየተካሄደ የሚገኘውም 45 ሺህ 542 አርሶ አደሮች በማሳተፍ እንደሆነ ጠቀሰው፤ የምርት አሰባሰቡ እስከ ሚያዝያ ወር አጋማሽ እንደሚቀጥል አስረድተዋል።

የሰንዴ ምርት በማይታወቅባቸው ቆላማ አካባቢዎች አሁን ላይ ከፍተኛ የስንዴ ምርት እየተገኘ መሆኑን ጠቁመው፤ ምርታማነቱም በሄክታር እስከ 45 ኩንታል መድረሱን አብራርተዋል።

የስንዴ ልማቱ ከውጭ የሚገባውን ከመተካት ባሻገር የምግብ ሉአላዊነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት አጋዥ ሚና እንዲጫወት ዞኑ የበኩሉን እየተወጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል።


ከሃብሩ ወረዳ አርሶ አደሮች ውስጥ አብዱ አራጋው በሰጡት አስተያየት፤ ባለፉት ሁለት ዓመታት በስንዴ ልማት በመሰማራታቸው ምርታማነታቸውን ማሳደግ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።

በዘንድሮ በጋም መስኖን በመጠቀም ከግማሽ ሄክታር በላይ ማሳቸውን በስንዴ በማልማት አሁን ላይ ሰብሉን ሰብስበው በመውቃት 19 ኩንታል ማግኘታቸውን ገልጸዋል።

የስንዴ ምርት በአካባቢ ገበያም ሆነ በምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች ተፈላጊነቱ ከፍተኛ በመሆኑ የልፋታችንን ዋጋ የሚከፍል አዋጭ ምርት ነው ብለዋል።

በዚሁ ወረዳ የቄስ ቀበሌ አርሶ አደር ሃይሉ ዳምጤ፤ ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ በመስኖ ያለሙት የበጋ ስንዴ አሁን ላይ እየታጨደ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

የሰንዴ ሰብሉን ያለሙት በሩብ ሄክታር መሬታቸው ላይ እንደሆነም አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.