
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2017(ኢዜአ)፦ የአምራች ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ቀልጣፋ የፋይናንስና የሎጂስቲክስ አገልግሎት ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ የተቋማት የስራ ኃላፊዎች ገለጹ።
በሶስተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ አራተኛ ቀን ውሎ "በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተቋማዊና ቅንጅታዊ አሰራር የአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነትና ተወዳዳሪነትን ማሳደግ" በሚል መሪ ሀሳብ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።

የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ በዚሁ ወቅት፤ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የጭነት ማጓጓዣ የጊዜና የገንዘብ ወጪ አፈፃጸም ለመቀነስ በተከናወነ የማሻሻያ ተግባር ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በዚህም ባለፉት አራት ዓመታት በታጁራ ወደብ ብቻ የኢንዱስትሪ ምርቶችን ጨምሮ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ጭነት በማጓጓዝ ከስድስት ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ማዳን እንደተቻለ አስረድተዋል።
የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋጋን በመቀነስና አሰራርን በማዘመን ቀጣይነት ባለው መልኩ የአምራች ኢንዱስትሪውን ለመደገፍ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።

የጉምሩክ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አዘዘው ጫኔ ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ አምራች ኢንዱስትሪና አስመጪዎች በልዩነት የሚስተናገዱበት የቀረጥና ታክስ ክፍያ የሕግና የአሰራር ማሻሻያ መደረጉን አስታውቀዋል።
በማሻሻያው አምራቾች የገንዘብ እጥረት ቢያጋጥማቸው ዋስትና በማስያዝ የማምረትና ዕቃ የማጓጓዝ ስራቸው ሳይደናቀፍ እስከ ሶስት ወር የሚስተናገዱበት አሰራር ተግባራዊ መደረጉን አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቤ ሳኖ በበኩላቸው፤ ባንኩ ባለፉት ሶስት ዓመት ከዘጠኝ ወር ብቻ ለአምራች ኢንዱስትሪ አንድ ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ድጋፍ አቅርቧል።
በበጀት ዓመቱ የተደረገው የውጭ ምንዛሬ ድጋፍ በ12 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ በቀጣይም ለአምራች ኢንዱስትሪው የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ አቅርቦት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ በሪሶ አመሎ(ዶ/ር)፤ ወደብ የደረሰ ገቢና ወጪ ምርት ከስምንት ቀን ባጠረ ጊዜ የማጓጓዝ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
አምራች ኢንዱስትሪውን ለመደገፍ በተደረገው ጥረትም የሎጂስቲክስ አገልግሎቱን ለማሳለጥ ከተለዩ 790 ድርጅቶች ውስጥ ለ509 አምራች ኢንዱስትሪዎች ልዩ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጅነር ጌቱ ገረመው፤ ለአምራች ኢንዱስትሪው በተመጣጣኝ ዋጋ የኃይል አቅርቦት በመስጠት ለሀገር ዕድገት ወሳኝ ሚና እንዲወጡ እየተደረገ ነው ብለዋል።
የኤሌክትሪክ ማከፋፈያ ማዕከላትንና ማስተላለፊያ መስመሮችን በማዘመን የኃይል አቅርቦት መቆራረጥ ችግሮችን መቀነስ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም አስታውቀዋል።
በውይይቱ የፋይናንስ፣ ጉምሩክ፣ ቴክኖሎጂና ቢዝነስ ድጋፍ፣ አገልግሎቶችን በመስጠት የአምራች ዘርፉን አስተማማኝ የሎጂስቲክስ አገልግሎት በመስጠት የግብዓትና ሸቀጦች ፍሰት ማሳለጥ እንዲሁም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን በመጠቀም አምራች ዘርፉ የሚያጋጥሙትን ችግሮችን መፍታት የሚሉት ጉዳዮች ተዳሰዋል።
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026
ጎንደር፤ መጋቢት 24/2018( ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚገኙ ከ239 ሺ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች በከተሞች የምግብ ዋስትና ስትራቴጂ ተ...
Apr 3, 2026
ደብረ ማርቆስ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ):-በምስራቅ ጎጃም ዞን ገበያውን ለማረጋጋት ከ169 ሚሊዮን ብር በላይ ተመድቦ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ የህብረት ሥራ...
Mar 31, 2026
ሀዋሳ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተኪ ምርት የማምረት አቅም በማሳደግ በሃገር ኢኮኖሚ ላይ ጉልህ ሚና እያበረከተ መሆኑን አምራ...
Mar 26, 2026